ጅቡቲ የነዳጅ ማጠራቀሚያ ዴፖ ለመገንባት የኢትዮጵያን የፋይናንስ ድጋፍ እየጠበቀች መሆኑን አስታወቀች
17:58 31.05.2026 (የተሻሻለ: 18:04 31.05.2026)

© telegram sputnik_ethiopia
ሰብስክራይብ
ጅቡቲ የነዳጅ ማጠራቀሚያ ዴፖ ለመገንባት የኢትዮጵያን የፋይናንስ ድጋፍ እየጠበቀች መሆኑን አስታወቀች
የጅቡቲ ወደቦችና ነፃ ቀጣናዎች ባለሥልጣን በዳመርጆግ ፈሳሽ ጭነት ወደብ የነዳጅ ማጠራቀሚያ ዴፖ ለመገንባት በመጪው የበጀት ዓመት የኢትዮጵያን ተሳትፎና ድጋፍ እየጠበቀ መሆኑን ይፋ አድርጓል።
የባለሥልጣኑ ሰብሳቢ አቡበከር ሀዲ ኡመር፤ ተቋማቸው ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ጋር ድርድር እያደረገ እንደሚገኝ ለሀገር ውስጥ የግል ሚዲያ ገልፀዋል።
የነዳጅ ማከማቻው ከኢትዮ-ጅቡቲ የባቡር መስመር 13 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ይገነባል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተመላክቷል።
ኢትዮጵያ እየተጠቀመችበት ያለው የ "ሆራይዘን ተርሚናል" አቅሙ መሙላቱን ተከትሎ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ጅቡቲ ውስጥ የነዳጅ ማጠራቀሚያ ለመገንባት 10 ሄክታር መሬት መጠየቁ የሚታወስ ነው።
ጅቡቲ በአፍሪካ ቀንድ እና በምስራቅ አፍሪካ ቁልፍ የኢነርጂ ማከፋፈያ መናኃሪያ ያደርጋታል የተባለ የ160 ሚሊዮን ዶላር ሁለገብ የነዳጅ ማከማቻ ማዕከል በስልታዊው የዳመርጆግ ኮሪደር ልትገነባ እንደሆነ ከዚህ በፊት ተዘግቧል፡፡
ስፑትኒክ ኢትዮጵያ | መተግበሪያ | X