በዚህ ዓመት ብቻ 69 አዳዲስ ሕገ-ወጥ ኬላዎች ተቋቁመዋል - የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር
18:23 13.11.2025 (የተሻሻለ: 18:24 13.11.2025)

© telegram sputnik_ethiopia
/ ሰብስክራይብ
በዚህ ዓመት ብቻ 69 አዳዲስ ሕገ-ወጥ ኬላዎች ተቋቁመዋል - የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር
በክልል መንግሥታት የተቋቋሙና በመላ ሀገሪቱ የምርቶች ነፃ እንቅስቃሴን እያደናቀፉ ያሉ ያልተፈቀዱ ኬላዎችን ለማፍረስ የሚወሰዱ ሕጋዊ እርምጃዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን በሚኒስቴሩ የወጪ ንግድ ፕሮሞሽን መሪ ሥራ አስፈፃሚ በቀለ ከተማ ለሀገር ውስጥ ሚዲያ ተናግረዋል፡፡
“ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ለአሠራር መሰናክል የሆኑትን እነዚህን ኬላዎች ለማስወገድ የፌደራልና የክልል አካላት በትብብር እንዲሠሩ መመሪያ ቢሰጡም አዳዲስ ኬላዎች መፈጠራቸውን ቀጥለዋል” ሲሉ አክለዋል፡፡
የክልል ኬላዎች ለደህንነት አስፈላጊ መሆናቸውን ያወሱት ኃላፊው፤ ከሕጋዊ ትዕዛዝ ውጭ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ግን ተቀባይነት የላቸውም ብለዋል፡፡
ኬላዎቹ መጀመሪያ ላይ ለደህንነት ተብለው የተቋቋሙ ቢሆንም አሁን ሕገ-ወጥ ንግድን በማበረታታትና የገበያ ትስስርን በማደናቀፍ ላይ በመሆናቸው ሚኒስቴሩ እርምጃ እንደሚወስድባቸው አፅንኦት ሰጥተዋል፡፡
የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር ባለፈው ዓመት 40 በመቶ የኢትዮጵያ ክፍል ላይ ያካሄደው ጥናት በመላ ሀገሪቱ 228 ያልተፈቀዱ ኬላዎች መኖራቸውን ያመለከተ ሲሆን አሁን 60 ያህሉ ፈርሰዋል ተብሏል፡፡
ስፑትኒክ ኢትዮጵያ | መተግበሪያ | X