የደቡብ ሱዳን የውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ኢትዮጵያን "የደቡብ ሱዳን አባት" ሲሉ መጥራታቸው ተዘገበ

የደቡብ ሱዳን የውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ኢትዮጵያን "የደቡብ ሱዳን አባት" ሲሉ መጥራታቸው ተዘገበ
ሚኒስትሩ አሌዩ አዪኒ አሌዩ፣ በትናንትናው ዕለት በደቡብ ሱዳን የኢትዮጵያ አምባሳደር ደሊል ከድር ጋር በድንበር ደህንነት እና በሁለትዮሽ ግንኙነት ዙሪያ ባደረጉት ከፍተኛ ደረጃ ውይይት፣ ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ2011 ሃገሪቱ ለተጎናፀፈችው ነጻነት ላበረከተችው ድጋፍ ከፍተኛ እውቅና ሰጥተዋል።
በተጨማሪም የደቡብ ሱዳን መንግሥት ከኢትዮጵያ ጋር "ዘላቂ ማኅበራዊ ግንኙነት፣ የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ ትብብር" ለመገንባት ቁርጠኛ መሆኗን ዳግም አረጋግጠዋል ሲሉ የደቡብ ሱዳን መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።
አምባሳደር ደሊል በበኩላቸው፣ ኢትዮጵያ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ታሪካዊ ግንኙነት ለመጠበቅ ቁርጠኛ እንደሆነች ገልጸው፣ አጋርነቱ በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ እና በሌሎች የትብብር ዓይነቶች እንደሚቀጥል እንዲሁም ግንኙነቱን በአስርተ ዓመታት የቆየ የጋራ ድጋፍ ላይ የተገነባ ነው ብለዋል።
በሱዳን የእርስ በርስ ጦርነቶች ወቅት ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ.የ1972ቱን የአዲስ አበባ ስምምነትን ጨምሮ በርካታ የሰላም ድርድር ዙሮችን አስተናግዳለች። በኋላም እ.ኤ.አ. በ2005ቱ አጠቃላይ የሰላም ስምምነት እና እ.ኤ.አ. በ2011 ደቡብ ሱዳን ነጻነቷን ለማግኘት የረዳውን የቀጠናዊ የሽምግልና ጥረት ቁልፍ ዲፕሎማሲያዊ ሚና ተጫውታለች።
ስፑትኒክ ኢትዮጵያ | መተግበሪያ | X