ኢትዮጵያ ከጥጥ ምርት ከ5 ቢሊዮን ዶላር በላይ የማግኘት አቅም እንዳላት ተገለጸ
20:02 08.01.2026 (የተሻሻለ: 20:04 08.01.2026)

© telegram sputnik_ethiopia
/ ሰብስክራይብ
ኢትዮጵያ ከጥጥ ምርት ከ5 ቢሊዮን ዶላር በላይ የማግኘት አቅም እንዳላት ተገለጸ
አገሪቱ እስከ 3 ሚሊዮን ሄክታር የሚደርስ ለጥጥ ልማት የሚውል መሬት ቢኖራትም፣ እስካሁን ጥቅም ላይ የዋለው ግን ከ3 እስከ 5 በመቶ ያህሉ ብቻ መሆኑን የኢትዮጵያ የጥጥ አምራቾች ማኅበር ዋና ዳይሬክተር ጸጋዬ አበበ ለስፑትኒክ አፍሪካ ተናግረዋል።
የዋጋ መለዋወጥ፣ የግብዓት ፋይናንስ እጥረት እና ጥራት ላይ ያተኮረ የገበያ ሥርዓት አለመኖር አምራቾችን ተስፋ በማስቆረጥ እንደ አገር በአግባቡ ካልተጠቀመንባቸው ዘርፎች መካከል አንዱ አድርጎታል ብለዋል፡፡
"ኢትዮጵያ ጥጥን ብትጠቀምበት ከቡናም ከወርቅም በላይ የውጭ ምንዛሬ የማግኘት አቅም አላት። ... ባህላዊ አልባሳቶቻችን ትልቅ ቅርስ ቢሆኑም ማዘመን ባለመቻላችን ቻይናዎች የእኛን ዲዛይን ኮፒ አድርገው እኛ በዓመት የምንሰራውን እነሱ በአንድ ቀን ሰርተው በርካሽ እየሸጡት ነው። ይሄ ደግሞ የቴክኖሎጂ እጥረት የፈጠረው ወደ ኋላ መቅረት ነው፡፡" ሲሉ ገልፀዋል፡፡
ዘርፉን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማገዝ ቢያንስ አሁን ያለውን ምርት በ10 በመቶ ማሳደግ ቢቻል፣ በሚቀጥሉት 5 ዓመታት ውስጥ እስከ 5 ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ማግኘት እንደሚቻልም ዋና ዳይሬክተሩ ጥናቶችን አጣቅሰው ጠቁመዋል።
በአሁኑ ወቅት ከ65 በላይ የንግድ እርሻዎች እና ከ500 ሺ በላይ አነስተኛ አምራቾች በዘርፉ የተሰማሩ ሲሆን፣ አገሪቱ ወደ ብሪክስ መቀላቀሏም ለዘርፉ አዲስ የገበያ ዕድል እንደሚከፍት ጸጋዬ አበበ አንስተዋል።
ምስል ከግብርና ሚኒስቴር
ስፑትኒክ ኢትዮጵያ | መተግበሪያ | X