ሶማሊያ የአፍሪካ ሕብረት የእስራኤልን የሶማሊላንድ እውቅና ውድቅ እንዲያደርግ አሳሰበች
12:07 07.01.2026 (የተሻሻለ: 12:14 07.01.2026)

© telegram sputnik_ethiopia
/ ሰብስክራይብ
ሶማሊያ የአፍሪካ ሕብረት የእስራኤልን የሶማሊላንድ እውቅና ውድቅ እንዲያደርግ አሳሰበች
የእስራኤል "የአንድ-ወገን እርምጃ"፣ የሶማሊያን ሉዓላዊነት አደጋ ላይ የሚጥል በመሆኑ የአፍሪካ ሀገራት በጋራ እንዲቃወሙት የሶማሊያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አብዲሰላም አብዲ አሊ ጥሪ አቀረቡ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሩ ይህንን ያስታወቀው ማክሰኞ ዕለት በተካሄደው የአፍሪካ ሕብረት የሰላምና ጸጥታ ምክር ቤት አስቸኳይ ስብሰባ ላይ ነው።
በሶማሊያ ጥያቄ የተጠራው ይህ ስብሰባ፣ እስራኤል ራሷን የቻለች ሀገር አድርጋ በቅርቡ እውቅና በሰጠቻት በተገንጣይዋ የሶማሊላንድ ክልል ጉዳይ ላይ ትኩረቱን ያደረገ ነበር።
ሚኒስትር አብዲሰላም ለምክር ቤቱ ሲናገሩ፣ "እንዲህ ያሉ እርምጃዎች የሶማሊያን ጊዜያዊ ሕገ-መንግሥት፣ የአፍሪካ ሕብረት መሥራች ስምምነትን እና የተመድ ቻርተርን የሚጥሱ ናቸው" ብለዋል። በተጨማሪም "ማንኛውም የውጭ አካል የአንድን የአፍሪካ ሕብረት አባል ሀገር የግዛት አንድነት የመለወጥ ሕጋዊ ስልጣን የለውም" ሲሉ አፅንዖት ሰጥተዋል።
የሶማሊያን አንድነት ማዳከም በአፍሪካ ቀንድ፣ በቀይ ባሕር እና በኤደን ባሕረ ሰላጤ ላይ አለመረጋጋት ሊፈጥር እንደሚችልና፣ ይህም በክልላዊ ደኅንነትና በፀረ-ሽብርተኝነት ትግል ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ እንደሚኖረው ሚኒስትሩ አስጠንቅቀዋል።
በስተመጨረሻም፣ የአፍሪካ ሕብረት አባላት የሶማሊያን ሉዓላዊነት በድጋሚ እንዲያረጋግጡ፣ የአፍሪካ አንድነትን መርሆዎች እና ዓለም አቀፍ ሕጎችን እንዲያስከብሩ ጥሪ አቅርበዋል።
ስፑትኒክ ኢትዮጵያ | መተግበሪያ | X