የምግብ እርዳታ ላልታለመለት አላማ እየዋለ የሚገኘው በተቀናጀ፣ በተደራጀ መንገድ መሆኑ ተገለጸ፤

ሰብስክራይብ
በኢትዮጵያ የሚገኙ ለጋሽ ድርጅቶች በጋራ ያዘጋጁት እና ለአዲስ ስታንዳርድ የደረሰው የውስጥ ማስታወሻ እንደሚያሳየው ከሆነ ድርጊቱ የተፈጸመው በትግራይ ብቻ አይደለም፤ ተግባሩ የፌደራል እና የክልል ተቋማትን ያሳተፈ በሰባት ክልሎች የተፈጸመ ነው። የአሜሪካ ተራድኦ ድርጅት ዩኤስኤድ ላለፉት ሁለት ወራት ባካሄደው ሰፊ ክትትል እና ምርመራ በኢትዮጵያ በለጋሽ ድርጅቶች የሚቀርብ የምግብ እርዳታ ላልታለመለት አላማ እየዋለ የሚገኘው በሀገር አቀፍ ደረጃ መሆኑን ማረጋገጡን የውስጥ ማስታወሻው አመላክቷል። ድርጊቱ በተቀናጀ መልኩ በተወሳሰበ የወንጀል መንገድ እንደሚፈጸም የጠቆመው ሰነዱ የምግብ እርዳታው ለተጎጂዎች እንዳይደርስ ድርጊቱ እንቅፋት መሆኑን አስታውቋል።
በኢትዮጵያ የሚንቀሳቀሱ የሰብአዊ እና መልሶ ማቋቋም ለጋሽ ድርጅቶች ቡድን በሰባት ክልሎች በሚገኙ 63 የዱቄት ፋብሪካዎች ላይ ያደረገው ክትትል እና ምርመራ የቀረቡ የምግብ እርዳታ እህሎች ላልታለመለት አላማ መዋሉን ማረጋገጡን በውስጥ ማስታወሻው ተጠቅሷል።
ተግባሩ የተፈጸመው የፌደራል እና የክልል ተቋማትን ባሳተፈ መልኩ መሁኑን የጠቆመው የምርመራ ውጤቱ ማስታወሻ የሀገሪቱ የመከላከያ ተቋም ክፍሎች ከሰብአዊ ረድኤቱ ተጠቃሚ እንዲሆኑ መደረጉን አመላክቷል። በዱቄት እና እህል ንግድ የተሰማሩ ግለሰቦች ተግባሩን በማመቻቸት ረገድ ሚና እንደነበራቸውም አስታውቋል።
የአሜሪካ ተራድኦ ድርጅት ዩኤስኤድ ባደረገው ክትትል ሌሎች ለጋሽ ሀገራት እና ድርጅቶች በሀገሪቱ ለሚገኙ ተጎጂዎች እንዲደርስ ያቀረቡት እርዳታ ላልታለመለት አላማ መዋሉን ማረጋገጡን ጠቁሟል። ከፈረንሳይ፣ ጃፓን እና ዩክሬን የተገኙ በአለም የምግብ ፕሮግራም አማካኝነት የቀረቡ እርዳታዎች ላልታለመለት አላማ መዋሉን ምርመራው ማረጋገጡን የውስጥ ማስታወሻው ላይ ተጠቅሷል።
እንደ ውስጥ ማስታወሻው ከሆነ የአሜሪካ ተራድኦ ድርጅት ዩኤስኤድ በመላ ሀገሪቱ የሚያካሂደውን የምግብ እርዳታ አቅርቦት ሊያቋርጥ የሚችልበት እድል ሰፊ መሆኑን ያሳያል። የአሜሪካን መንግስት በ2022 ብቻ የአንድ ነጥብ ስምንት ቢሊየን ዶላር የህይወት አድን እርዳታ መለገሱ ይታወሳል።
ምንም እንኳ የተራድኦ ድርጅቱ የረድኤት ማቋረጥ ውሳኔ ምግብ ነክ ያልሆኑ እርዳታዎች ላይ ተጽእኖ ባይኖረውም ከዚህ በኋላ በአሜሪካ መንግስት እገዛ የሚካሄዱ ቀጣይ እርዳታዎች ከመከፋፈላቸው በፊት የሀገሪቱ የሰብአዊ ረድኤት ተደራሽነት አሰራር አስቸኳይ እና አስፈላጊ የመዋቅር ማሻሻያ ማድረግ እንደሚጠበቅበት ተገልጿል።
አዳዲስ ዜናዎች
0